Home Back

​ቭላድሚር ፑቲን ሰሜን ኮሪያን ሊጎበኙ ነው

voanews.com 2024/10/5
ፎቶ ፋይል፦ የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን
ፎቶ ፋይል፦ የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን

የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ለሁለት ቀናት ጉብኝት ማክሰኞ ሰሜን ኮሪያ እንደሚገቡ የሰሜን ኮሪያ የመንግሥት ብዙኀን መገናኛ ዘግቧል።

ፑቲን በቆይታቸው ከሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ ኡን ጋራ እንደሚገናኙ እና፣ ከዋሽንግተን ጋራ ያላቸው ልዩነት እና ቅራኔ እየሰፋ በመጣበት ወቅት ወታደራዊ ትብብራቸውን በሚያጠናክሩበት መንገድ ላይ እንደሚወያዩ ይጠበቃል።

የሰሜን ኮሪያ ማዕከላዊ የዜና አገልግሎት ሰኞ እለት እንዳስታወቀው፣ ፑቲን ማክሰኞ እና ረቡዕ በሰሜን ኮሪያ ጉብኝት የሚያደርጉት በኪም ጆንግ ኡን በቀረበላቸው ግብዣ መሠረት ነው። የሰሜን ኮሪያ ሚዲያው ስለጉብኝቱ ተጨማሪ ዝርዝሮችን ባይሰጥም፣ ፑቲን ጉብኝቱን እንደሚያደርጉ ሩሲያ አረጋግጣለች።

ፑቲን ሰሜን ኮሪያን የሚጎበኙት ከ24 ዓመት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲኾን ጉብኝታቸውን የሚያደርጉት፣ ፒዮንግያንግ ሞስኮ በዩክሬን ለምታደርገው ጦርነት እየሰጠች ያለችው የጦር መሳሪያ ድጋፍ የሚፈጥረው ዓለም አቀፍ ስጋት እየጨምረ በሄደበት ወቅት ነው። ሰሜን ኮሪያ በምትኩ የኢኮኖሚ ድጋፍ እና የኪምን የኒዩክሌር ጦር እና ሚሳይል ፕሮግራም የሚያሳድግ የቴኮኖሎጂ ልውውጥ ታገኛለች።

ኪም በመስከረም ወር ወደ ሩሲያ ሩቅ ምስራቅ ተጉዘው ከፑቲን ጋራ ከተገናኙ በኋላ ሁለቱ ሀገራት የሚደርጉት ወታደራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ሌሎች ትብብሮች እየጨምረ መሄዱ ተገልጿል።

የዩናይትድ ስቴትስ እና ድቡብ ኮሪያ ባለሥልጣናት፣ ሰሜን ኮሪያ ለሩሲያ በምትሰጠው የመድፍ፣ የሚሳይል እና ሌሎች ወታደራዊ ቁሳቁሶች ድጋፍ በዩክሬን ያለውን ጦርነት እንዲራዘም ድጋፍ አድርጋለች ሲሉ ክስ ያቀርቡባታል። ፒዮንግያንግ እና ሞስኮ ግን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ውሳኔዎችን የሚጥሰውን የጦር መሳሪያ ዝውውር ውንጀላ ውድቅ አድርገዋል።

People are also reading