Home Back

ደቡብ ኮሪያ፣ ቻይና እና ጃፓን ከአራት ዓመት በኃላ ለመጀመሪያ ጊዜ የሦስትዮሽ ስብሰባ ሊያደርጉ ነው

voanews.com 2024/6/29
የደቡብ ኮርያ ፕሬዝዳንት ዩን ሶክ ዪኦል፣ የቻይና ጠቅላይ ሚኒስትር ሊ ቺያንግ እና የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ፉሚዮ ኪሺዳ
የደቡብ ኮርያ ፕሬዝዳንት ዩን ሶክ ዪኦል፣ የቻይና ጠቅላይ ሚኒስትር ሊ ቺያንግ እና የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ፉሚዮ ኪሺዳ

የደቡብ ኮሪያ፣ ቻይና እና ጃፓን መሪዎች ትብብራቸውን እንዴት ማደስ እንደሚችሉ ለመምከር ከአራት ዓመት በኃላ ለመጀመሪያ ጊዜ ተገናኝተው የሦስትዮሽ ውይይት ሊያደርጉ መሆኑን የደቡብ ኮሪያ ፕሬዝዳንታዊ ጽህፈት ቤት ሐሙስ እለት አስታውቋል።

የሦስቱ አገራት መሪዎች እ.አ.አ በ2008 ከአካሄዱት የመጀመሪያ ሦስትዮሽ ስብሰባ በኃላ፣ በየዓመቱ ለመገናኘት ተስማምተው የነበረ ቢሆንም፣ እ.አ.አ በ2019 ቻይና ላይ ከተካሄደው የመጨረሻው ስብሰባ ወዲህ በኮቪድ 19 ወረርሽኝ እና በእስያ ጎረቤት አገሮች መካከል በተፈጠረው ውስብስብ ግንኙነት ምክንያት ተቋርጦ ቆይቷል።

የደቡብ ኮርያ ፕሬዝዳንት ዩን ሶክ ዪኦል፣ የቻይና ጠቅላይ ሚኒስትር ሊ ቺያንግ እና የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ፉሚዮ ኪሺዳ የሚያካሂዱት የሦስትዮሽ ስብሰባ ሰኞ በደቡብ ኮሪያ ዋና ከተማ ሲዮል ውስጥ የሚጀመር ሲሆን የቻይና ፕሬዝዳንት ዢ ጂንፒንግ እንደማይገኙ፣ የሲዮል ምክትል ብሔራዊ የደህንነት ዳይሬክተር ኪም ቴሄዮ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግረዋል።

"ጉባዔው የኮሪያ፣ የጃፓንን እና ለቻይናን የሦስትዮሽ ትብብር ወደነበረበት ለመመለስ እና መደበኛ ለማድረግ የለውጥ ምዕራፍ ይሆናል" ያሉት ኪም ሦስቱ መሪዎች ደቡብ ኮሪያ ባቀረበቻቸው የሰራተኛ ልውውጥ፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ ንግድ፣ ጤና፣ ቴክኖሎጂ እና አደጋዎች የመሳሰሉ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ እንደሚወያዩ አመልክተዋል።

ኪም አክለው ሦስቱ መሪዎቹ ይፋ ባልተደረጉ ቀጠናዊ እና ዓለማቀፋዊ የፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ፣ እንዲሁም ለዓለም አቀፍ የፖሊሲ ቀውሶች እና ዓለም አቀፍ ሰላም እንዴት በጋራ ምላሽ መስጠት እንደሚችሉም ይወያያሉ ብለዋል።

በባህል እና በኢኮኖሚ የቀረበ ትስስር ያላቸው ሦስቱ አገራት፣ ከዓለም አቀፉ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት 25 ከመቶውን ይሸፍናሉ።

People are also reading