Home Back

በ20 ሀገራት የአውሮፓ ህብረት ምክር ቤት አባላት ምርጫ እየተካሄደ ነው

voanews.com 2024/7/4
በሃንጋሪ የቡዳፔስት ነዋሪ ለአውሮፓ ህብረት ምክር ቤት አባላትና ለሀገር ውስጥ ምርጫ እኤአ ሰኔ 9 2024 ድምጽ ሲሰጡ
በሃንጋሪ የቡዳፔስት ነዋሪ ለአውሮፓ ህብረት ምክር ቤት አባላትና ለሀገር ውስጥ ምርጫ እኤአ ሰኔ 9 2024 ድምጽ ሲሰጡ

የአውሮፓ ህብረት ፓርላማን ወደ ቀኝ ወገንተኞቹ ያዞራል ተብሎ ለሚጠበቀው ምርጫ፣ ዛሬ እሁድ በ20 የአውሮፓ ሀገራት መራጮች 720 የምክር ቤት አባላትን ለመምረጥ ድምጽ ሲሰጡ ውለዋል፡፡

የዩክሬን ጦርነት፣ ስደት እና የአየር ንብረት ፖሊሲ በገበሬዎች ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ፣ መራጮች ላይ ተጽእኖ ያሳድራሉ ከተባሉ ቁልፍ ጉዳዮች መካከል ይገኙበታል።

ዋና ዋናዎቹ እና የአውሮፓ ህብረት ደጋፊ ፓርቲዎች አብላጫቸውን ይዘው እንደሚቀጥሉ ቢጠበቅም ፣ እንደ ኔዘርላንዱ ገርት ዊልደርስ እና ፈረንሳዩ ማሪን ለፔን የሚመሯቸው ጠንካራዎቹ ቀኝ ፓርቲዎች መቀመጫዎችን ሊያገኙ እንደሚችሉ ተገምቷል።

በምክር ቤቱ የጠንካራ ቀኝ ፓርቲዎች ውክልና መጨመር፣ በአውሮፓ ህብረት ውስጥ፣ ህጎችን ማውጣት እና ውሳኔዎችን ሊያወሳስብ ይችላል ተብሏል፡፡

የአውሮፓ ህብረት ህግ አውጪዎች፣ በፋይናንስ ህጎች፣ የአየር ንብረት እና የግብርና ፖሊሲ ላይ ተጽዕኖ ያሳድራሉ፤ የአውሮፓ ህብረት በጀትን ያፀድቃሉ እንዲሁም በአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን ሹመቶች ላይ ድምጽን በድምጽ የመሻር ስልጣን ይይዛሉ።

መራጮች 450 ሚሊዮን የአውሮፓ ነዋሪዎችን በሚወክለው በምክር ቤቱ ላይ ያላቸው እምነት፣ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ፣ በኢኮኖሚ ውድቀት እና በዩክሬን ጦርነት በደረሰበት ቀውስ ተሸርሽሯል፡፡

የቤልጂየም ጠቅላይ ሚኒስትር አሌክሳንደር ዴክሮ አውሮፓ ወሳኝ ደረጃ ላይ እና ከፍተኛ ጫና ውስጥ እንደምትገኝ አስጠንቅቀዋል፡፡

ቀኝ አክራሪዎቹ ወይም ህዝባዊ ፓርቲዎች አሁን በሃንጋሪ፣ ስሎቫኪያ እና ጣሊያን መንግስታትን እየመሩ ሲሆን፣ በሌሎች ሀገራት ውስጥም የገዥው ጥምረት አካል ናቸው።

በዚህ ምርጫ የህግ ረቂቆችን የሚያቀርበውን እና የአውሮፓ ህብረት ገንዘቦችን ፣ የንግድ እና የውድድር ፖሊሲዎችን የሚቆጣጠረው የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን ፕሬዝዳንትን፣ የአውሮፓ ህብረት የውጭ ፖሊሲ ኃላፊን ጨምሮ ሌሎች አዳዲስ የአውሮፓ ህብረት መሪዎች ይመረጣሉ ።

People are also reading