Home Back

ለጋሽ ሃገራት ለኢትዮጵያ መንግሥት ማሳሰቢያ ሰጡ

voanews.com 2024/5/17
ፎቶ ፋይል፦ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት፣ ጀኒቫ ስዊዘርላንድ
ፎቶ ፋይል፦ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት፣ ጀኒቫ ስዊዘርላንድ

"የኢትዮጵያ አጋር እና ወዳጅ ሃገራት” የተሰኘው ስብስብ፣ በሀገሪቱ የርዳታ ሠራተኞችን ጨምሮ በአጠቃላይ ሲቪሎች ጥበቃ እንዲደረግላቸውና በአዲስ አበባ ያለው መንግሥት በመላ ሃገሪቱ ሠላም ለማስፈን እንዲጥር ጠይቀዋል።

ስብስቡ በመጪው ማክሰኞ ጀኒቫ ውስጥ የሚደረገውንና፣ በኢትዮጵያ ላለው ሰብአዊ ቀውስ የሚሰጥ ርዳታ እወጃ ሥነ ሥርዓትን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ፣ የሚሰጠው ርዳታ እጅግ ለተጎዱት ወገኖች እንዲደርስና፣ ላልታሰበለት ዓላማ እንዳይውል ለማረጋገጥ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ተጠያቂነትን እንዲያሰፍን አሳስበዋል።

በስብስቡ ውስጥ የተካተቱት ሃገራት፤ እንግሊዝ፣ አውሮፓ ኅብረት፣ አውስትራሊያ፣ ቤልጂየም፣ ካናዳ፣ ዴንማርክ፣ ፊንላንድ፣ ፈረንሣይ፣ ጀርመን፣ አየርላንድ፣ ጣሊያን፣ ለክሰምበርግ፣ ኔዘርላንድስ፣ ኒው ዚላንድ፣ ኖርዌ፣ ስዊዲንና አሜሪካ መሆናቸው ታውቋል።

የጀኒቫውን ስብሰባም የኢትዮጵያ መንግሥት፣ የተመድ የሰብአዊ ርዳታ ማስተባበሪያ ቢሮ (ኦቻ) እና የእንግሊዝ መንግሥት በጋራ እንደሚመሩትም ታውቋል።

“ግጭት፣ የኢኮኖሚ መንኮታኮት፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና የበሽታዎች ወረርሽን በመሰሉና ተነባብረው በሚከሰቱ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ምክንያት፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ለአስደንጋጭ የምግብ ዋስትና ዕጦትና የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ተጋልጠዋል” ብሏል ስብስቡ ባወጣው መግለጫ።

ለሰብአዊ አግልግሎት የሚውል ገንዘብ ለማግኘት ሃገራት በሚራኮቱበት ወቅት፣ ባለፈው ዓመት በኢትዮጵያ የርዳታ እህል መመዝበሩ፣ የለጋሾችን መተማመን የሸረሸረ ክስተት ነበር ሲል ስብስቡ በመግለጫው አክሏል።

People are also reading