Home Back

የሙቀት ማዕበልን ያካተተ ከባድ የአየር ኹኔታ ዩናይትድ ስቴትስን አስግቷል

voanews.com 2024/7/7
ፊኒክስ ውስጥ ያለውን ከፍተኛ የሙቀት መጠን በመቋቋም በማለዳ የእግር ጉዞ እያጠናቀቀ ፊኒክስ፤ እአአ ነሃሴ 11/2019፣
ፊኒክስ ውስጥ ያለውን ከፍተኛ የሙቀት መጠን በመቋቋም በማለዳ የእግር ጉዞ እያጠናቀቀ ፊኒክስ፤ እአአ ነሃሴ 11/2019፣

በዚኽ ሳምንት፣ ሙቀትንና ቅዝቃዜን ያካተተ ከባድ የአየር ኹኔታ፣ በዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ ይከሠታል ተብሎ እንደሚጠበቅ፣ የአሜሪካ ባለሥልጣናት አስጠንቅቀዋል።

የዩናይትድ ስቴትስ ደቡብ ምዕራብ ነዋሪዎች፣ ወደ ምሥራቅ እየተጓዘ ከሚገኘው ከፍተኛ የሙቀት ሞገድ እንዲጠነቀቁ ያሳሰቡት ባለሥልጣናቱ፣ ከፍተኛ ዝናም እና ጎርፍ በባሕር ዳርቻ የሚገኙ የዩናይትድ ስቴትስ ግዛቶችን ሊያጥለቀልቅ እንደሚችልና በሰሜን ምዕራብ የሚገኙ ተራራማ ስፍራዎችን ደግሞ በረዶ እንደሚያሰጋቸው ጠቁመዋል።

በአሜሪካ ልዩ ልዩ አካባቢዎች የሚታዩት ከባድ የአየር ኹኔታዎች እየጨመሩ በሔዱበት ወቅት፤ ከፍተኛ ሙቀት በአሪዞና፣ ኒው ሜክሲኮ እና ሌሎች የቴክሳስ፣ የኮሎራዶ እና የካንሳስ ግዛት አካባቢዎች ተስፋፍቷል። ብሔራዊው የአየር ኹኔታ አገልግሎት፣ ትላንት እሑድ እንዳስታወቀው፣ ከ63 ሚሊዮን በላይ ሰዎች የከፍተኛ ሙቀት ማስጠንቀቂያ ደርሷቸዋል።

ፊኒክስ በሚገኘው ብሔራዊው የአየር ኹኔታ አገልግሎት የአየር ሁኔታ ትንበያ ባለሞያ የኾኑት ቴድ ዊቶክ፣ “በአካባቢያችን ጉልሕ የኾነ ከፍተኛ ሙቀት አይተናል፤” ያሉ ሲኾን፣ ማስጠንቀቂያዎቹ በተሰጠባቸው አካባቢዎች፣ ማንኛውም ሰው ከጠዋቱ አራት ሰዓት እስከ ምሽቱ 12 ሰዓት ባለው ጊዜ ከቤት እንዳይወጣ፣ ውኃ እንዲጠጣና ቀለል ያለ ምቹ ልብስ እንዲለብስ መክረዋል።

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ፣ በፊኒክስ የሙቀት መጠኑ በከፍተኛ ኹኔታ እየጨመረ ሲሔድ፣ እ.አ.አ በ2023 ብቻ 645 ሰዎች ከሙቀት ጋራ በተገናኘ አደጋ ሕይወታቸው አልፏል።

በሌላ በኩል፣ በስተሰሜን በሚገኙ ተራራማ አካባቢዎች፣ ሰኞ እና ማክሰኞ በረዶ እንደሚጥል የሚጠበቅ ሲኾን፣ በአንዳንድ የሞንታና እና ሰሜን-ማዕከላዊ አይዳሆ አካባቢዎች ደግሞ፣ የከፍተኛ አውሎ ነፋስ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል።

People are also reading